ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ነገሥት 17:32-41 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

32. እግዚአብሔርን አመለኩ፤ ይሁን እንጂ እያንዳንዱ ወገን የመጣበትን ሕዝብ ልማድ ተከትሎ፣ በየኰረብታው ባሉት ቤተ ጣዖታት የሚያገለግሉትን ካህናት ሾመ።

33. በአንድ በኩል እግዚአብሔርን ሲያመልኩ፣ በሌላ በኩል ግን እንደየአገራቸው ልማድ የየራሳቸውን አማልክት ያመልኩ ነበር።

34. ይህንንም ልማዳቸውን እስከ ዛሬ ድረስ አልተውትም፤ እግዚአብሔርን በአግባቡ አያመልኩም፤ እንዲሁም እስራኤል ብሎ ለጠራው ለያዕቆብ ዘሮች የሰጣቸውን ሥርዐቶችና ደንቦች፣ ሕጎችና ትእዛዞችን አይከተሉም።

35. እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ጋር ኪዳን ሲገባ እንዲህ ሲል አዞአቸው ነበር፤ “ሌሎችን አማልክት አታምልኳቸው፤ አትስገዱላቸው፤ አታገልግሏቸው፤ አትሠውላቸውም፤

36. ማምለክ የሚገባችሁ ግን በታላቅ ኀይልና በተዘረጋች ክንድ ከግብፅ ምድር ያወጣችሁን እግዚአብሔርን ብቻ ነው። ለእርሱ ስገዱ፤ ለእርሱም መሥዋዕት አቅርቡ።

37. የጻፈላችሁን ሥርዐቶችና ደንቦች፣ ሕጎችና ትእዛዞች ምንጊዜም ተግታችሁ ጠብቁ። ሌሎች አማልክትን አታምልኩ።

38. ከእናንተ ጋር የገባሁትን ኪዳን አትርሱ፤ ሌሎች አማልክትም አታምልኩ።

39. ይልቅስ አምላካችሁን እግዚአብሔርን አምልኩ፤ ከጠላቶቻችሁ ሁሉ እጅ የሚታደጋችሁ እርሱ ነውና።”

40. ነገር ግን በቀደመው ልማዳቸው ጸኑ እንጂ አልተመለሱም።

41. እነዚህ ሕዝቦች ምንም እንኳ በአንድ ወገን እግዚአብሔርን ቢያመልኩት የተቀረጹ ምስሎቻቸውንም ያገለግሉ ነበር። ልጆቻቸውና የልጅ ልጆቻቸውም አባቶቻቸው ያደረጉትን ዛሬም እንደ ቀጠሉበት ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ነገሥት 17