ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 103:10-22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. እንደ ኀጢአታችን አልመለሰልንም፤እንደ በደላችንም አልከፈለንም።

11. ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፣እንዲሁ ለሚፈሩት ምሕረቱ ታላቅ ናት።

12. ምሥራቅ ከምዕራብ እንደሚርቅ፣መተላለፋችንን በዚያው መጠን ከእኛ አስወገደ።

13. አባት ለልጆቹ እንደሚራራ፣ እግዚአብሔር ለሚፈሩት እንዲሁ ይራራል።

14. እርሱ አፈጣጠራችንን ያውቃልና፤ትቢያ መሆናችንንም ያስባል።

15. ሰው እኮ ዘመኑ እንደ ሣር ነው፤እንደ ዱር አበባ ያቈጠቍጣል፤

16. ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ግን ድራሹ ይጠፋል፤ምልክቱም በቦታው አይገኝም።

17. የእግዚአብሔር ምሕረት ግን፣ከዘላለም እስከ ዘላለም በሚፈሩት ላይ ነው፤ጽድቁም እስከ ልጅ ልጅ ድረስ በላያቸው ይሆናል፤

18. ኪዳኑን በሚጠብቁት ላይ፣ትእዛዙንም ለመፈጸም በሚተጉት ላይ ይሆናል።

19. እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አጽንቶአል፤መንግሥቱም ሁሉን ትገዛለች።

20. እናንተ ለቃሉ የምትታዘዙ መላእክቱ፤ትእዛዙንም የምትፈጽሙ እናንተ ኀያላን፤ እግዚአብሔርን ባርኩ።

21. እናንተ ፈቃዱን የምትፈጽሙ አገልጋዮቹ፤ሰራዊቱ ሁሉ፣ እግዚአብሔርን ባርኩ።

22. እናንተ በግዛቱ ሁሉ የምትኖሩ፣ፍጥረቱ ሁሉ፣ እግዚአብሔርን ባርኩ፤ነፍሴ ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኪ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 103