ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 77:10-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. እኔም፣ “የልዑል ቀኝ እጅ እንደ ተለወጠ ማሰቤ፣ይህ ድካሜ ነው” አልሁ።

11. የእግዚአብሔርን ሥራ አስታውሳለሁ፤የጥንት ታምራትህን በእርግጥ አስታውሳለሁ፤

12. ሥራህን ሁሉ አሰላስላለሁ፤ድንቅ ሥራህን ሁሉ አውጠነጥናለሁ።

13. አምላክ ሆይ፤ መንገድህ ቅዱስ ነው፤እንደ አምላካችን ያለ ታላቅ አምላክ ማን ነው?

14. ታምራትን የምታደርግ አምላክ አንተ ነህ፤በሕዝቦችም መካከል ኀይልህን ትገልጣለህ።

15. የያዕቆብንና የዮሴፍን ልጆች፣ሕዝብህን በክንድህ ተቤዠሃቸው። ሴላ

16. አምላክ ሆይ፤ ውሆች አዩህ፤ውሆች አንተን አይተው ተሸማቀቁ፤ጥልቆችም ተነዋወጡ።

17. ደመናት ውሃን አንጠባጠቡ፤ሰማያት አንጐደጐዱ፤ፍላጾችህም ዙሪያውን አብለጨለጩ።

18. የነጐድጓድህ ድምፅ በዐውሎ ነፋስ ውስጥ ተሰማ፤መብረቅህ ዓለምን አበራው፤ምድርም ራደች፤ ተንቀጠቀጠች።

19. መንገድህ በባሕር ውስጥ ነው፤መሄጃህም በታላቅ ውሃ ውስጥ ነው፤ዱካህ ግን አልታወቀም።

20. በሙሴና በአሮን እጅ፣ሕዝብህን እንደ በግ መንጋ መራኸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 77