ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ናሆም 3 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ለነነዌ

1. ለደም ከተማ ወዮላት!ሐሰት፣ዘረፋም ሞልቶባታል፤ብዝበዛዋ ተግዞ አያልቅም።

2. የጅራፍ ድምፅ፣የመንኰራኵር ኳኳቴ፣የፈጣን ፈረስ ኮቴ፣የሠረገሎች ድምፅ ተሰምቶአል

3. ፈረሰኛው ይጋልባል፤ሰይፍ ይንቦገቦጋል፤ጦር ያብረቀርቃል፤የሞተው ብዙ ነው፤ሬሳ በሬሳ ሆኖአል፤ስፍር ቍጥር የለውም፤መተላለፊያ አልተገኘም።

4. ይህ ሁሉ የሆነው ቅጥ ባጣች፣አሳሳችና መተተኛ በሆነች ዘማዊት ምክንያት ነው፤እርሷም በዝሙቷ አሕዛብን፣በጥንቈላዋም ሕዝቦችን ባሪያ ያደረገች ናት።

5. የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“እኔ በጠላትነት ተነሥቼብሻለሁ፤ቀሚስሽን እስከ ፊትሽ እገልበዋለሁ፤ዕርቃንሽን ለአሕዛብ፣ኀፍረትሽንም ለነገሥታት አሳያለሁ።

6. ቍሻሻ እደፋብሻለሁ፤እንቅሻለሁ፤ማላገጫም አደርግሻለሁ።

7. የሚያዩሽ ሁሉ ከአንቺ እየሸሹ፣‘ነነዌ ፈራርሳለች፤ ማን ያለቅስላታል?’ ይላሉ፤የሚያጽናናሽንስ ከወዴት አገኛለሁ?”

8. አንቺ በዐባይ ወንዝ አጠገብ ካለችው፣በውሃ ከተከበበችው፣ከኖእ አሞን ትበልጫለሽን?ወንዙ መከላከያዋ፣ውሃውም ቅጥሯ ነው።

9. ኢትዮጵያና ግብፅ ወሰን የለሽ ኀይሏ ናቸው፤ፉጥና ሊቢያም ረዳቶቿ ነበሩ።

10. ይሁን እንጂ በምርኮ ተወሰደች፤ተሰዳም ሄደች።በየመንገዱ ማእዘን ላይ፣ሕፃናቷ ተፈጠፈጡ፤በመሳፍንቷ ላይ ዕጣ ተጣለ፤ታላላቅ ሰዎቿ ሁሉ በሰንሰለት ታሰሩ።

11. አንቺ ደግሞ ትሰክሪያለሽ፤ትደበቂያለሽ፣ከጠላትም መሸሸጊያ ትፈልጊያለሽ።

12. ምሽጎችሽ ሁሉ ሊበሉ እንደ ደረሱየመጀመሪያ በለስ ፍሬ ናቸው፤በሚወዛወዙበት ጊዜ፣ፍሬዎቹ በበላተኛው አፍ ውስጥ ይወድቃሉ።

13. እነሆ፤ ጭፍሮችሽ፣ሁሉም ሴቶች ናቸው!የምድርሽ በሮች፣ለጠላቶችሽ ወለል ብለው ተከፍተዋል፤መዝጊያዎቻቸውንም እሳት በልቶአቸዋል።

14. ለከበባው ውሃ ቅጂ፤መከላከያሽን አጠናክሪ፤የሸክላውን ዐፈር ፈልጊ፤ጭቃውን ርገጪ፤ጡቡንም ሥሪ።

15. በዚያ እሳት ይበላሻል፤ሰይፍ ይቈርጥሻል፤እንደ ኵብኵባም ይግጥሻል።እንደ ኵብኵባ እርቢ፤እንደ አንበጣም ተባዢ።

16. ከሰማይ ከዋክብት እስኪበልጡ ድረስ፣የነጋዴዎችሽን ቊጥር አበዛሽ፤ምድሪቱን ግን እንደ አንበጣ ግጠው አሟጠጡ፤ከዚያም በረው ሄዱ።

17. ጠባቂዎችሽ እንደ አንበጣ፣መኳንንቶችሽም በብርድ ቀንበቅጥር ሥር እንደሚቀመጥ ኵብኵባ ናቸው፤ፀሓይ ሲወጣ ግን ይበራሉ፤የት እንደሚበሩም አይታወቅም።

18. የአሦር ንጉሥ ሆይ፤ እረኞችህ አንቀላፉ፤መኳንንትህ ዐርፈው ተኙ፤ሕዝብህ ሰብሳቢ አጥተው፣በተራራ ላይ ተበትነዋል።

19. ቊስልህን ሊፈውስ የሚችል የለም፤ስብራትህም ለሞት የሚያደርስ ነው፤ስለ አንተ የሰማ ሁሉ፣በውድቀትህ ደስ ብሎት ያጨበጭባል፤ወሰን የሌለው ጭካኔህ፣ያልነካው ማን አለና?