ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 14:1-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ስለ ድርቅ ወደ ኤርምያስ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው፤

2. “ይሁዳ ታለቅሳለች፤ከተሞቿም ይማቅቃሉ፤በምድር ላይ ተቀምጠው ይቈዝማሉ፤ጩኸትም ከኢየሩሳሌም ወጥቶ ይሰማል።

3. መሳፍንት አገልጋዮቻቸውን ውሃ ፍለጋ ይሰዳሉ፤እነርሱ ወደ ውሃ ጒድጓዶች ይወርዳሉ፤ነገር ግን ውሃ አያገኙም፤ዐፍረውና ተስፋ ቈርጠው፣ራሳቸውን ተከናንበው፣ባዶ እንስራ ይዘው ይመለሳሉ።

4. በምድሪቱ ዝናብ ስለሌለ፣መሬቱ ተሰነጣጥቆአል፤ገበሬዎችም ዐፍረው፣ራሳቸውን ተከናንበዋል።

5. አንዳች ሣር ባለመኖሩ፣የሜዳ አጋዘን እንኳ፣እንደ ወለደች ግልገሏን ጥላ ትሄዳለች።

6. የሜዳ አህዮች ባድማ ኰረብቶች ላይ ቆሙ፤እንደ ቀበሮም አየር ፍለጋ አለከለኩ፤ግጦሽ ባለመገኘቱ፣ዐይኖቻቸው ፈዘዙ።”

7. እግዚአብሔር ሆይ፤ ከአንተ መኰብለል አብዝተናል፤በአንተም ላይ ዐምፀናል፤ኀጢአታችን ቢመሰክርብንም እንኳ፣ስለ ስምህ ብለህ አንድ ነገር አድርግልን።

8. አንተ የእስራኤል ተስፋ፤በጭንቀት ጊዜ አዳኙ፣ለምን በምድሪቱ እንደ ባዕድ፣እንደ ሌት አዳሪ መንገደኛ ትሆናለህ?

9. ግራ እንደ ተጋባ ሰው፣ለመታደግም ኀይል እንዳጣ ተዋጊ ትሆናለህ? እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ በመካከላችን አለህ፤በስምህም ተጠርተናል፤እባክህ አትተወን።

10. እግዚአብሔር ስለዚህ ሕዝብ እንዲህ ይላል፤“መቅበዝበዝ እጅግ ይወዳሉ፤እግሮቻቸው አይገቱም፤ስለዚህ እግዚአብሔር በእነርሱ ደስ አይለውም፤አሁን በደላቸውን ያስባል፤በኀጢአታቸውም ይቀጣቸዋል።”

11. እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፤ “ለዚህ ሕዝብ በጎነት አትጸልይ፤

12. ቢጾሙም ጩኸታቸውን አልሰማም፤ የሚቃጠል መሥዋዕትና የእህል ቍርባን ቢያቀርቡም አልቀበላቸውም፤ ነገር ግን በሰይፍ፣ በራብና በቸነፈር አጠፋቸዋለሁ።”

13. እኔም፣ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ ወዮ!፣ ነቢያቱ ‘ሰይፍ አታዩም፤ ራብም አያገኛችሁም፤ ነገር ግን በዚህ ስፍራ ዘለቄታ ያለው ሰላም እሰጣችኋለሁ’ ይላል ይሏቸዋል” አልሁ።

14. እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፤ “ነቢያቱ በስሜ የሐሰት ትንቢት ይናገራሉ፤ እኔ አልላክኋቸውም፤ አላዘዝኋቸውም፤ አልተናገርኋቸውምም። የሐሰት ራእይ፣ ሟርት፣ ከንቱ ነገርንና የልባቸውን ሽንገላ ይተነብዩላችኋል።

15. ስለዚህ በስሜ የሐሰት ትንቢት ስለሚናገሩ ነቢያት እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ እኔ ሳልልካቸው፣ ‘ሰይፍና ራብ በዚች ምድር ላይ አይመጣም’ የሚሉ እነዚህ ነቢያት በሰይፍና በራብ ይጠፋሉ፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 14