ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 24:1-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በለዓምም እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤልን መባረክ እንደ ወደደ ባየ ጊዜ፣ እንደ ሌላው ጊዜ ሁሉ አስማት ለመሻት አልሄደም፤ ነገር ግን ፊቱን ወደ ምድረ በዳ መለሰ።

2. በለዓም አሻግሮ ተመልክቶ እስራኤል በየነገድ በየነገዱ ሆኖ መስፈሩን ሲያይ የእግዚአብሔር (ኤሎሂም) መንፈስ በላዩ መጣበት፤

3. ንግሩንም እንዲህ ሲል ጀመረ፤“የዚያ ዐይኑ የተከፈተለት፣የቢዖር ልጅ የበለዓም ንግር፣

4. የዚያ የአምላክን (ኤሎሂም) ቃል የሚሰማ፣ሁሉን የሚችል የአምላክን ራእይ የሚያይ፣ከመሬት የተደፋው ዐይኖቹም የተከፈቱለት ሰው ንግር፤

5. “ያዕቆብ ሆይ፤ ድንኳኖችህ፣እስራኤል ሆይ፤ ማደሪያዎችህ እንዴት ያማሩ ናቸው!

6. “እንደ ሸለቆዎች፣በወንዝ ዳር እንዳሉም የአትክልት ስፍራዎች ተዘርግተዋል፤ በእግዚአብሔር (ያህዌ) እንደ ተተከሉ ሬቶች፣በውሃም አጠገብ እንዳሉ ዝግባዎች ናቸው።

7. ከማድጋቸው ውሃ ይፈሳል፤ዘራቸውም የተትረፈረፈ ውሃ ያገኛል፤“ንጉሣቸው ከአጋግ ይልቃል፤መንግሥታቸውም ከፍ ከፍ ይላል፤

8. “እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ከግብፅ አወጣቸው፤ብርታታቸውም እንደ ጎሽ ብርታት ነው፤ጠላቶች የሆኑአቸውን ሕዝብ ያነክታሉ፤ዐጥንቶቻቸውን ያደቅቃሉ፤በፍላጾቻቸው ይወጓቸዋል።

9. እንደ አንበሳ አድፍጠዋል፤እንደ እንስቲቱም አንበሳ አድብተዋል፤ ሊቀሰቅሳቸውስ የሚችል ማን ነው?“የሚባርኩህ ቡሩክ፣የሚረግሙህም ርጉም ይሁኑ።”

10. ከዚያም ባላቅ፣ በበለዓም ላይ እጅግ ተቈጣ፤ እጆቹንም አጨብጭቦ እንዲህ አለው፤ “ጠላቶቼን እንድትረግምልኝ ጠራሁህ፤ አንተ ግን ሦስቱንም ጊዜ ባረክሃቸው።

11. በል ቶሎ ወደ ቤትህ ሂድልኝ፤ ወሮታህን አሳምሬ ልከፍልህ ነበር፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) ግን እንዳታገኝ ከለከለህ።”

12. በለዓምም ለባላቅ እንዲህ ሲል መለሰለት፤ ወደ እኔ ለላክሃቸው ሰዎች እንዲህ ብዬ ነግሬአቸው አልነበረምን?

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 24