ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 32:31-42 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

31. የጋድና የሮቤል ሰዎች እንዲህ ሲሉ መለሱለት፤ “ባሪያዎችህ እግዚአብሔር (ያህዌ) ያለውን ያደርጋሉ፤

32. ለጦርነት ዝግጁ ሆነን በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወደ ከነዓን እንሻገራለን፤ የምንወርሰው ርስት ግን ከዮርዳኖስ ወዲህ እዚሁ ይሆናል።”

33. ከዚያም ሙሴ፣ የአሞራውያንን ንጉሥ የሴዎንን ግዛትና የባሳንን ንጉሥ የዐግን ግዛት ማለትም ምድሪቱንና ከነከተሞቿ በዙሪያዋ ያለውን ግዛት በሙሉ ለጋድና ለሮቤል ነገዶች እንዲሁም ለዮሴፍ ልጅ ለምናሴ ነገድ እኩሌታ ሰጣቸው።

34. የጋድ ልጆች፤ ዲቦንን፣ አጣሮትን፣ አሮዔርን፣

35. ዓጥሮትሾፋንን፣ ኢያዜርን፣ ዮግብሃን፣

36. ቤትነምራንና ቤትሃራንን የተመሸጉ ከተሞች አድርገው ሠሩአቸው፤ እንዲሁም ለበግና ለፍየል መንጎቻቸው ጒረኖዎች አበጁላቸው።

37. የሮቤልም ልጆች ሐሴቦንን፣ ኤልያሊንና ቂርያታይምን

38. እንዲሁም ስማቸው የተለወጠውን ናባውን፣ በአልሜዎንን፣ ሴባማንን ዐደሱ፤ ላደሷቸውም ከተሞች ስም አወጡላቸው።

39. የምናሴ ልጅ የሆነው የማኪር ዘሮች ወደ ገለዓድ ሄደው ምድሪቱን በመያዝ፣ እዚያ የነበሩትን አሞራውያን አሳደዱአቸው፤

40. ስለዚህ ሙሴ ገለዓድን የምናሴ ዘሮች ለሆኑት ለማኪራውያን ሰጣቸው፤ እነርሱም መኖሪያቸውን በዚያው አደረጉ።

41. ከምናሴ ነገድ የሆነው ኢያዕር መኖሪያቸውን ወስዶ፣ “የኢያዕር መንደሮች” ብሎ ሰየማቸው።

42. እንዲሁም ኖባህ ቄናትንና በዙሪያዋ ያሉትን መንደሮች በመያዝ በራሱ ስም፣ “ኖባህ” ብሎ ጠራቸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 32