ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 9:16-23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. ይህ በዚህ ሁኔታ ቀጠለ፤ ደመናው ማደሪያውን ሸፈነው፤ በሌሊትም የእሳት መልክ ነበረው።

17. ደመናው ከድንኳኑ ላይ በሚነሣበት ጊዜ እስራኤላውያን ጒዞአቸውን ይጀምሩ ነበር፤ ደመናው በሚቆምበት ቦታ ደግሞ ይሰፍሩ ነበር፤

18. እስራኤላውያን ጒዞ የሚጀምሩትም ሆነ የሚሰፍሩት በእግዚአብሔር (ያህዌ) ትእዛዝ ነበር። ደመናው በድንኳኑ ላይ በሚቈይበት ጊዜ ሁሉ ከሰፈር አይንቀሳቀሱም ነበር።

19. ደመናው በድንኳኑ ላይ ብዙ ቀን ቢቈይም እስራኤላውያን የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ትእዛዝ ይጠብቃሉ እንጂ ተነሥተው አይጓዙም።

20. አንዳንድ ጊዜ ደመናው በድንኳኑ ላይ የሚቈየው ለጥቂት ቀን ብቻ ነበር፤ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ትእዛዝ ይሰፍራሉ፤ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ትእዛዝ ጒዞ ይጀምራሉ፤

21. አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ደመናው ከምሽት እስከ ንጋት ብቻ ይቈያል፤ ደመናው ንጋት ላይ ሲነሣም ጒዞአቸውን ይጀምራሉ፤ ቀንም ይሁን ሌሊት ደመናው ከተነሣ ጒዞ ይጀምራሉ።

22. ደመናው በድንኳኑ ላይ ለሁለት ቀንም ይሁን ለወር ወይም ለዓመት ቢቈይ፣ እስራኤላውያን በሰፈር ይቈያሉ እንጂ ጒዞአቸውን አይቀጥሉም።

23. በእግዚአብሔር (ያህዌ) ትእዛዝ ይሰፍራሉ፤ በእግዚአብሔርም (ያህዌ) ትእዛዝ ይጓዛሉ፤ እነርሱም በሙሴ አማካይነት የተሰጠውን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ይጠብቁ ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 9