ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 16:6-16 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. አብራምም፣ “አገልጋይሽ እንደሆነች በእጅሽ ውስጥ ናት፤ የፈለግሽውን አድርጊባት” አላት። ከዚያም ሦራ ስላሠቃየቻት አጋር ጥላት ኰበለለች።

7. የእግዚአብሔር (ያህዌ) መልአክ አጋርን በአንድ የውሃ ምንጭ አጠገብ በምድረ በዳ አገኛት፤ ምንጩም ወደ ሱር በሚወስደው መንገድ ዳር ነበር።

8. መልአኩም፣ “የሦራ አገልጋይ አጋር ሆይ፤ ከየት መጣሽ? ወዴትስ ትሄጃለሽ?” አላት፤እርሷም፣ “ከእመቤቴ ከሦራ ኰብልዬ መምጣቴ ነው” ብላ መለሰች።

9. የእግዚአብሔርም (ያህዌ) መልአክ፣ “ወደ እመቤትሽ ተመለሽ፤ ለእርሷም ተገዥላት” አላት።

10. ደግሞም መልአኩ፣ “ዘርሽን እጅግ አበዛለሁ፤ ከብዛቱም የተነሣ ሊቈጠር አይችልም” አላት።

11. የእግዚአብሔርም (ያህዌ) መልአክ በተጨማሪ እንዲህ አላት፤“እነሆ፤ ፀንሰሻል፤ወንድ ልጅ ትወልጃለሽ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) ችግርሽን ተመልክቶአል፤ስሙን እስማኤል ትዪዋለሽ።

12. እርሱም እንደ ዱር አህያ ይሆናል፤እጁንም ባገኘው ሰው ሁሉ ላይ ያነሣል፤ያገኘውም ሁሉ እጁን ያነሣበታል፤ከወንድሞቹ ሁሉ ጋር እንደ ተጣላ ይኖራል።”

13. እርሷም ያናገራትን እግዚአብሔርን (ያህዌ)፣ ኤልሮኢ ብላ ጠራችው፤ ምክንያቱም “የሚያየኝን አሁን አየሁት” ብላ ነበርና።

14. ከዚህ የተነሣ የዚያ ምንጭ ስም፣ “ብኤርለሃይሮኢ” ተብሎ ተጠራ፤ እስካሁንም በቃዴስና በባሬድ መካከል ይገኛል።

15. አጋር ለአብራም ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ አብራምም ስሙን እስማኤል ብሎ ጠራው።

16. አብራም፣ አጋር እስማኤልን በወለደች ጊዜ ዕድሜው 86 ዓመት ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 16