ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 24:45-57 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

45. “በልቤ የምጸልየውን ጸሎት ገና ሳልጨርስ፣ ርብቃ እንስራዋን በትከሻዋ ላይ አድርጋ ብቅ አለች፤ ወደ ምንጩም ወርዳ ውሃ ቀዳች። እኔም፣ ‘እባክሽ፤ ውሃ አጠጪኝ’ አልኋት።

46. “እርሷም ፈጥና እንስራዋን ከትከሸዋ አውርዳ፣ ‘ጠጣ፤ ግመሎችህንም አጠጣለሁ’ አለች። እኔም ጠጣሁ፤ ግመሎቹንም አጠጣች።

47. “ለመሆኑ የማን ልጅ ነሽ” ብዬ ጠየቅኋት።“እርሷም፣ ‘ሚልካ ለናኮር የወለደችለት፣ የባቱኤል ልጅ ነኝ’ አለችኝ።“ከዚያም ቀለበቱን አደረግሁላት፤ አምባሩንም በእጇ አስገባሁላት።

48. ተደፍቼም ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰገድሁ፤ ለጌታዬ ወንድም የልጅ ልጅ የሆነችውን ቈንጆ፣ ለጌታዬ ልጅ እንዳገኝለት በቀና መንገድ የመራኝ የጌታዬ የአብርሃምን አምላክ እግዚአብሔርን (ኤሎሂም ያህዌ) አመሰገንሁ።

49. እንግዲህ አሁን ለጌታዬ በጎነትና ታማኝነት የምታሳዩ ከሆነ ሐሳባችሁን አስታውቁኝ፤ ካልሆነ ግን ቍርጡን ንገሩኝና የምሄድበትን ልወስን።”

50. ላባና ባቱኤል እንዲህ ሲሉ መለሱ፤ “ነገሩ ከእግዚአብሔር (ያህዌ) ስለ ሆነ በዚህም ሆነ በዚያ ምንም ማለት አንችልም።

51. ርብቃ ይቻትልህ፤ ይዘሃት ሂድ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) እንደ ተናገረው ለጌታህ ልጅ ሚስት ትሁነው።”

52. የአብርሃም አገልጋይ ያሉትን በሰማ ጊዜ በምድር ላይ ተደፍቶ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰገደ።

53. ከዚያም የወርቅና የብር ጌጣጌጥ፣ እንዲሁም ልብሶች አውጥቶ ለርብቃ ሰጣት፤ ደግሞም ለወንድሟና ለእናቷ ከፍ ያለ ዋጋ ያላቸው ስጦታዎች ሰጣቸው።

54. እርሱና አብረውት የነበሩ ሰዎችም በልተው፣ ጠጥተው እዚያው ዐደሩ፤በማግስቱ ጠዋት ሲነሡ፣ የአብርሃም አገልጋይ፣ “እንግዲህ ወደ ጌታዬ እንድመለስ አሰናብቱኝ” አለ።

55. ወንድሟና እናቷም፣ “ልጂቷ ከእኛ ጋር ቢያንስ ዐሥር ቀን ያህል ትቈይና ከዚያ በኋላ ልትሄድ ትችላለች።” ብለው መለሱ።

56. እርሱ ግን፣ “እግዚአብሔር (ያህዌ) መንገዴን አቅንቶልኛልና አታዘግዩኝ፤ ወደ ጌታዬ እንድመለስ አሰናብቱኝ” አላቸው።

57. እነርሱም፣ “ለማናቸውም ልጂቱን እንጥራትና ትጠየቅ” አሉ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 24