ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ራእይ 14:8-17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. ሌላም ሁለተኛ መልአክ፣ “ሕዝቦች ሁሉ የዝሙቷን ቍጣ ወይን ጠጅ እንዲጠጡ ያደረገች ታላቂቱ ባቢሎን ወደቀች ወደቀች!” እያለ ተከተለው።

9. ሦስተኛውም መልአክ በታላቅ ድምፅ እንዲህ እያለ ተከተላቸው፤ “ማንም ለአውሬውና ለምስሉ የሚሰግድ፣ ምልክቱንም በግምባሩ ወይም በእጁ ላይ የሚቀበል ቢኖር፣

10. እርሱ ደግሞ ምንም ነገር ሳይቀላቀልበት በቍጣው ጽዋ ውስጥ የተሞላውን የእግዚአብሔርን ቍጣ ወይን ጠጅ ይጠጣል። በቅዱሳን መላእክትና በበጉ ፊትም በእሳትና በዲን ይሠቃያል።

11. የሥቃያቸውም ጢስ ከዘላለም እስከ ዘላለም ወደ ላይ ይወጣል። ለአውሬውና ለምስሉ የሚሰግዱ ወይም የስሙንም ምልክት የሚቀበሉ ሁሉ ቀንና ሌሊት ዕረፍት የላቸውም።”

12. የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁና ለኢየሱስም ታማኝ ሆነው በትዕግሥት የሚጸኑ ቅዱሳን የሚታወቁት በዚህ ነው።

13. ከዚያም፣ “ከእንግዲህ ወዲህ በጌታ ሆነው የሚሞቱ ብፁዓን ናቸው ብለህ ጻፍ” የሚል ድምፅ ከሰማይ ሰማሁ። መንፈስም፣ “አዎ፣ ሥራቸው ስለሚከተላቸው ከድካማቸው ያርፋሉ” ይላል።

14. አየሁም፤ እነሆ፤ በፊቴ ነጭ ደመና ነበረ፤ በደመናውም ላይ፣ “የሰውን ልጅ የሚመስል” ተቀምጦ ነበር፤ እርሱም በራሱ ላይ የወርቅ አክሊል ደፍቶ፣ በእጁም ስለታም ማጭድ ይዞ ነበር።

15. ሌላም መልአክ ከመቅደሱ ወጥቶ በደመናው ላይ ለተቀመጠው፣ “የዐጨዳው ሰዓት ስለ ደረሰ፣ ማጭድህን ይዘህ ዕጨድ፤ የምድር መከር ደርሶአልና” ሲል በታላቅ ድምፅ ጮኸ።

16. ስለዚህ በደመናው ላይ የተቀመጠው ማጭዱን ወደ ምድር ሰደደ፤ ምድርም ታጨደች።

17. ሌላም መልአክ በሰማይ ካለው መቅደስ ወጣ፤ እርሱም እንዲሁ ስለታም ማጭድ ነበረው፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ራእይ 14