ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 119:113-126 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

113. መንታ ልብ ያላቸውን ጠላሁ፤ሕግህን ግን ወደድሁ።

114. አንተ መጠጊያዬና ጋሻዬ ነህ፤ቃልህን በተስፋ እጠብቃለሁ።

115. የአምላኬን ትእዛዛት እጠብቅ ዘንድ፣እናንት ክፉ አድራጊዎች፣ ከእኔ ራቁ።

116. እንደ ቃልህ ደግፈኝ፤ እኔም ሕያው እሆናለሁ፤ተስፋዬም መና ቀርቶ አልፈር።

117. ያለ ሥጋት እቀመጥ ዘንድ ደግፈህ ያዘኝ፤ሥርዐትህንም ዘወትር እመለከታለሁ።

118. መሰሪነታቸው በከንቱ ነውና፣ከሥርዐትህ ውጭ የሚሄዱትን ሁሉ ወዲያ አስወገድሃቸው።

119. የምድርን ክፉዎች ሁሉ እንደ ጥራጊ አስወገድሃቸው፤ስለዚህ ምስክርህን ወደድሁ።

120. ሥጋዬ አንተን በመፍራት ይንቀጠቀጣል፤ፍርድህንም እፈራለሁ።

121. ፍትሕና ጽድቅ ያለበትን ሠርቻለሁ፤ለሚጨቍኑኝ አሳልፈህ አትስጠኝ።

122. ለባሪያህ በጎነት ዋስትና ሁን፤እብሪተኛ እንዲጨቍነኝ አትፍቀድላቸው።

123. ዐይኖቼ ማዳንህን፣የጽድቅ ቃልህን በመጠባበቅ ደከሙ።

124. ለባሪያህ እንደ ምሕረትህ መጠን አድርግ፤ሥርዐትህንም አስተምረኝ።

125. እኔ ባሪያህ ነኝ፤ምስክርነትህን ዐውቅ ዘንድ ማስተዋልን ስጠኝ።

126. እግዚአብሔር ሆይ፤ሕግህ እየተጣሰ ነውና፣ጊዜው አንተ የምትሠራበት ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 119