ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 119:139-155 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

139. ጠላቶቼ ቃልህን ዘንግተዋልና፣ቅናት አሳረረኝ።

140. ቃልህ እጅግ የነጠረ ነው፤ባሪያህም ወደደው።

141. እኔ ታናሽና የተናቅሁ ነኝ፤ነገር ግን መመሪያህን አልዘነጋሁም።

142. ጽድቅህ ዘላለማዊ ጽድቅ ነው፤ሕግህም እውነት ነው።

143. መከራና ሥቃይ ደርሶብኛል፤ነገር ግን ትእዛዝህ ደስታዬ ነው።

144. ምስክርነትህ ለዘላለም የጽድቅ ምስክርነት ነው፤በሕይወት እኖር ዘንድ ማስተዋልን ስጠኝ።

145. እግዚአብሔር ሆይ፤ በፍጹም ልቤ እጮኻለሁና መልስልኝ፤ሥርዐትህንም እጠብቃለሁ።

146. ወደ አንተ እጣራለሁና አድነኝ፤ምስክርነትህንም እጠብቃለሁ።

147. ትረዳኝ ዘንድ ጎሕ ሳይቀድ ተነሥቼ እጮኻለሁ፤ቃልህንም ተስፋ አደርጋለሁ።

148. ቃልህን አሰላስል ዘንድ፣ዐይኔ ሌሊቱን ሙሉ ሳይከደን ያድራል።

149. እንደ ቸርነትህ መጠን ድምፄን ስማ፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ እንደ ሕግህ መልሰህ ሕያው አድርገኝ።

150. ደባ የሚያውጠነጥኑ ወደ እኔ ቀርበዋል፤ከሕግህ ግን የራቁ ናቸው።

151. እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ግን ቅርብ ነህ፤ትእዛዛትህም ሁሉ እውነት ናቸው።

152. ለዘላለም እንደ መሠረትሃቸው፣ከጥንት ምስክርነትህ ተረድቻለሁ።

153. ሕግህን አልረሳሁምና፣ ሥቃዬን ተመልከት፤ ታደገኝም።

154. ተሟገትልኝ፤ አድነኝም፤እንደ ቃልህም ሕያው አድርገኝ።

155. ሥርዐትህን ስለማይሹ፣ድነት ከክፉዎች የራቀ ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 119