ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 119:32-48 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

32. ልቤን አስፍተህልኛልና፣በትእዛዛትህ መንገድ እሮጣለሁ።

33. እግዚአብሔር ሆይ፤ የሥርዐትህን መንገድ አስተምረኝ፤እኔም እስከ መጨረሻው እጠብቀዋለሁ።

34. ሕግህን እንድጠብቅ፣ በፍጹም ልቤም እንድታዘዘው፣ ማስተዋልን ስጠኝ።

35. በእርሷ ደስ ይለኛልና፣በትእዛዝህ መንገድ ምራኝ።

36. ከራስ ጥቅም ይልቅ፣ልቤን ወደ ምስክርነትህ አዘንብል።

37. ከንቱ ነገር ከማየት ዐይኖቼን መልስ፤በራስህ መንገድ እንደ ገና ሕያው አድርገኝ።

38. ትፈራ ዘንድ፣ለአገልጋይህ የገባኸውን ቃል ፈጽም።

39. የምፈራውን መዋረድ ከእኔ አርቅ፤ደንብህ መልካም ነውና።

40. እነሆ፤ ድንጋጌህን ናፈቅሁ፤በጽድቅህ ሕያው አድርገኝ።

41. እግዚአብሔር ሆይ፤ ምሕረትህ ወደ እኔ ይምጣ፤ማዳንህም እንደ ቃልህ ይላክልኝ።

42. በቃልህ ታምኛለሁና፣ለሚሰድቡኝ መልስ እሰጣለሁ።

43. ሕግህን ተስፋ አድርጌአለሁና፣የእውነትን ቃል ከአፌ ፈጽመህ አታርቅ።

44. ከዘላለም እስከ ዘላለም፣ሕግህን ዘወትር እጠብቃለሁ።

45. ሥርዐትህን እሻለሁና፣እንደ ልቤ ወዲያ ወዲህ እመላለሳለሁ።

46. ምስክርነትህን በነገሥታት ፊት እናገራለሁ፤ይህን በማድረግም ዕፍረት አይሰማኝም።

47. እኔ እወደዋለሁና፣በትእዛዝህ ደስ ይለኛል።

48. እጆቼን ወደምወዳቸው ትእዛዛትህ አነሣለሁ፤ሥርዐትህንም አሰላስላለሁ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 119