ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 119:45-61 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

45. ሥርዐትህን እሻለሁና፣እንደ ልቤ ወዲያ ወዲህ እመላለሳለሁ።

46. ምስክርነትህን በነገሥታት ፊት እናገራለሁ፤ይህን በማድረግም ዕፍረት አይሰማኝም።

47. እኔ እወደዋለሁና፣በትእዛዝህ ደስ ይለኛል።

48. እጆቼን ወደምወዳቸው ትእዛዛትህ አነሣለሁ፤ሥርዐትህንም አሰላስላለሁ።

49. ለአገልጋይህ የገባኸውን ቃል ዐስብ፤በዚያ ተስፋ ሰጥተኸዋልና።

50. ቃልህ ሕያው ያደርገኛልና፣ይህች በመከራዬ መጽናኛዬ ናት።

51. እብሪተኞች እጅግ ተሣለቁብኝ፤እኔ ግን ከሕግህ ንቅንቅ አልልም።

52. እግዚአብሔር ሆይ፤ ከጥንት የነበረውን ድንጋጌህን ዐሰብሁ፤ በዚህም ተጽናናሁ።

53. ሕግህን ከተዉ ክፉዎች የተነሣ፣ቍጣ ወረረኝ።

54. በእንግድነቴ አገር፣ሥርዐትህ መዝሙሬ ናት።

55. እግዚአብሔር ሆይ፤ ስምህን በሌሊት ዐስባለሁ፤ሕግህንም እጠብቃለሁ።

56. ሥርዐትህን እከተላለሁ፤ይህችም ተግባሬ ሆነች።

57. እግዚአብሔር ዕድል ፈንታዬ ነው፤ቃልህን ለመታዘዝ ቈርጫለሁ።

58. በፍጹም ልቤ ፊትህን ፈለግሁ፤እንደ ቃልህ ቸርነትህን አሳየኝ።

59. መንገዴን ቃኘሁ፤አካሄዴንም ወደ ምስክርህ አቀናሁ።

60. ትእዛዝህን ለመጠበቅ፣ቸኰልሁ፤ አልዘገየሁምም።

61. የክፉዎች ገመድ ተተበተበብኝ፤ እኔ ግን ሕግህን አልረሳሁም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 119