ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 37:23-38 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

23. የሰው አካሄድ በእግዚአብሔር ይጸናል፤በመንገዱ ደስ ይለዋል።

24. ቢሰናከልም አይወድቅም፤ እግዚአብሔር በእጁ ደግፎ ይይዘዋልና።

25. ጐልማሳ ነበርሁ፤ አሁን አርጅቻለሁ፤ነገር ግን ጻድቅ ሲጣል፣ዘሩም እንጀራ ሲለምን አላየሁም።

26. ሁል ጊዜ ቸር ነው፤ ያበድራልም፤ልጆቹም የተባረኩ ይሆናሉ።

27. ከክፉ ራቅ፤ መልካሙንም አድርግ፤ለዘላለምም ትኖራለህ።

28. እግዚአብሔር ፍትሕን ይወዳልና፤ታማኞቹንም አይጥልም፤ለዘላለምም ይጠብቃቸዋል፤የኀጢአተኛው ዘር ግን ይጠፋል።

29. ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፤በእርሷም ለዘላለም ይኖራሉ።

30. የጻድቅ አፍ ጥበብን ይናገራል፤አንደበቱም ፍትሐዊ ነገር ያወራል።

31. የአምላኩ ሕግ በልቡ አለ፤አካሄዱም አይወላገድም።

32. ክፉዎች ጻድቁን ይከታተሉታል፤ሊገድሉትም ይሻሉ።

33. እግዚአብሔር ግን በእጃቸው አይጥለውም፤ፍርድ ፊት ሲቀርብም አሳልፎ አይሰጠውም።

34. እግዚአብሔርን ደጅ ጥና፤መንገዱንም ጠብቅ፤ምድሪቱን ትወርስ ዘንድ ከፍ ከፍ ያደርግሃል፤ክፉዎችም ሲጠፉ ታያለህ።

35. ክፉና ጨካኙን ሰው፣እንደ ሊባኖስ ዝግባ ለምልሞ አየሁት፤

36. ዳግመኛ በዚያ ሳልፍ፣ እነሆ፣ በቦታው አልነበረም፤ብፈልገውም አልተገኘም።

37. ንጹሐንን ልብ በል፤ ቅኑንም አስተውል፤የሰላም ሰው ተስፋ አለውና።

38. ኀጢአተኞች ግን በአንድነት ይጠፋሉ፤የክፉዎችም ዘር ይወገዳል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 37