ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 17:8-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. በውሃ ዳር እንደ ተተከለ፣ሥሩንም ወደ ወንዝ እንደ ሰደደ ዛፍ ነው፣ሙቀት ሲመጣ አይፈራም፤ቅጠሉም ዘወትር እንደለመለመ ነው፤በድርቅ ዘመን አይሠጋም፤ፍሬ ማፍራቱንም አያቋርጥም።”

9. የሰው ልብ ከሁሉ ይልቅ ተንኰለኛ ነው፤ፈውስም የለውም፤ማንስ ሊረዳው ይችላል?

10. “እኔ እግዚአብሔር ለሰው ሁሉ እንደ መንገዱ፣እንደ ሥራው ፍሬ ለመስጠት፣ልብን እመረምራለሁ፤የአእምሮንም ሐሳብ እፈትናለሁ።”

11. ሀብትን በግፍ የሚያከማች ሰው፣ያልፈለፈለችውን ጫጩት እንደምትታቀፍ ቆቅ ነው፤በዕድሜው አጋማሽ ትቶት ይሄዳል፤በመጨረሻም ሞኝነቱ ይረጋገጣል።

12. የመቅደሳችን ስፍራ፣ከጥንት ጀምሮ ከፍ ያለ የክብር ዙፋን ነው።

13. የእስራኤል ተስፋ እግዚአብሔር ሆይ፤ጥለውህ የሚሄዱ ሁሉ ያፍራሉ፤ፊታቸውን ከአንተ የሚመልሱ በምድር ውስጥ ይጻፋሉ፤የሕይወትን ውሃ ምንጭ፣ እግዚአብሔርን ትተዋልና።

14. እግዚአብሔር ሆይ፤ ፈውሰኝ፤ እፈወሳለሁ፤አድነኝ እኔም እድናለሁ፤አንተ ምስጋናዬ ነህና።

15. እነርሱ ደጋግመው፣“የእግዚአብሔር ቃል የት አለ?እስቲ አሁን ይፈጸም!” ይሉኛል።

16. እረኛ ሆኜ አንተን ከማገልገል ወደ ኋላ አላልሁም፤ክፉ ቀን እንዳልተመኘሁ ታውቃለህ፤ከአንደበቴ የሚወጣውም በፊትህ ግልጽ ነው።

17. አስደንጋጭ አትሁንብኝ፤በመከራ ቀን መሸሸጊያዬ አንተ ነህ።

18. አሳዳጆቼ ይፈሩ፤እኔን ግን ከዕፍረት ጠብቀኝ፤እነርሱ ይደንግጡ፤እኔን ግን ከድንጋጤ ሰውረኝ፤ክፉ ቀን አምጣባቸው፤በዕጥፍ ድርብ ጥፋት አጥፋቸው።

19. እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፤ “ሄደህ የይሁዳ ነገሥታት በሚገቡበትና በሚወጡበት በሕዝቡ በር በሌሎቹም የኢየሩሳሌም በሮች ሁሉ ቁም፤

20. እንዲህም በላቸው፤ ‘በእነዚህ በሮች የምትገቡ የይሁዳ ነገሥታት ሆይ፤ የይሁዳ ሕዝብና በኢየሩሳሌም የምትኖሩ ሁሉ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ።

21. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “በሰንበት ቀን ሸክም ተሸክማችሁ በኢየሩሳሌም በሮች እንዳታስገቡ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።

22. አባቶቻችሁን እንዳዘዝኋቸው ሰንበትን አክብሩ እንጂ በሰንበት ቀን ከየቤታችሁ ሸክም ይዛችሁ አትውጡ፤ ምንም ሥራ አትሥሩ።”

23. እነርሱ ግን አልሰሙም፤ ልብም አላሉም፤ እንዳይሰሙና እንዳይገሠጹም ዐንገታቸውን አደነደኑ።

24. ነገር ግን በጥንቃቄ ብት ታዘዙኝ ይላል እግዚአብሔር፤ በሰንበትም ቀን በዚህች ከተማ በሮች ሸክም ይዛችሁ ባትገቡ፣ የሰንበትንም ቀን ምንም ሳትሠሩ ብትቀድሱት፣

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 17