ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 14:3-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. እግዚአብሔር (ያህዌ) ወደዚች ምድር የሚያመጣን ለምንድ ነው? በሰይፍ እንድንወድቅ ነውን? ሚስቶቻችንና ልጆቻችንም ይማረካሉ፤ ታዲያ ወደ ግብፅ መመለሱ አይሻለንም?”

4. እርስ በርሳቸውም፣ “አለቃ መርጠን ወደ ግብፅ እንመለስ” ተባባሉ።

5. ከዚያም ሙሴና አሮን እዚያ በተሰበሰቡት በመላው እስራኤላውያን ማኅበር ፊት በግንባራቸው ተደፉ።

6. ምድሪቱን ከሰለሏት መካከል የነበሩት የነዌ ልጅ ኢያሱና የዩፎኒ ልጅ ካሌብ ልብሳቸውን ቀደዱ፤

7. ለመላው የእስራኤል ማኅበርም እንዲህ አሉ፤ “ዞረን ያየናትና የሰለልናት ምድር እጅግ ሲበዛ መልካም ናት።

8. እግዚአብሔር (ያህዌ) በእኛ ደስ ከተሰኘብን ማርና ወተት ወደምታፈሰው ወደዚያች ምድር መርቶ ያገባናል፤ ለእኛም ይሰጠናል።

9. ብቻ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ላይ አታምፁ፤ እንደ እንጀራ እንጐርሳቸዋለንና የምድሪቱን ሰዎች አትፍሩአቸው። ጥላቸው ተገፎአል፤ እግዚአብሔርም (ያህዌ) ከእኛ ጋር ነውና አትፍሯቸው።”

10. መላው ማኅበር ግን በድንጋይ ሊወግሯቸው ተነጋገሩ፤ ከዚያም የእግዚአብሔር (ያህዌ) ክብር በመገናኛው ድንኳን ለእስራኤላውያን ሁሉ ተገለጠ።

11. እግዚአብሔርም (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ይህ ሕዝብ እስከ መቼ ይንቀኛል” እነዚህን ሁሉ ታምራት በመካከሉ እያደረግሁ የማያምንብኝስ እስከ መቼ ነው?

12. በቸነፈር እመታዋለሁ፤ እደመስሰዋለሁም፤ አንተን ግን ብርቱና ታላቅ ለሆነ ሕዝብ አደርግሃለሁ።”

13. ሙሴ እግዚአብሔርን (ያህዌ) እንዲህ አለው፤ “ነገሩን ግብፃውያን ቢሰሙትስ! ይህን ሕዝብ በኀይልህ ከመካከላቸው አውጥተኸዋልና፤

14. የተደረገውንም በዚች ምድር ለሚኖሩት ሰዎች ይነግሯቸዋል። እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፣ አንተ ከዚህ ሕዝብ ጋር መሆንህን፣ ደግሞም አንተ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሆይ፤ ፊት ለፊት እንደታየህና ደመናህ በላያቸው እንደሆነ፣ አንተም ቀን በደመና ዐምድ ሌሊትም በእሳት ዐምድ እፊት እፊታቸው እየሄድህ እንደ መራሃቸው ቀድሞውኑ ሰምተዋል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 14